Tuesday 9 July 2019

ከስልጠን ጀርባ የድብቅነት ስነልቡና አባዜ

ጌታቸው መላኩ (የሚዲያና ተግባቦት አማካሪ)
በ getachewmelaku@gmail.com ላይ ሊያገኙአቸው ይችላሉ፡፡

በትርክት ሰምተን ከፅሁፍ ሰነዶች አንብበን፣ ነገር ግን ልክ እንደኖርንበት ጊዜ የምናውቀው (ከጊዜው ቅርበት የተነሳ ይመስለኛል) የቀዳማዊ ሀይለስላሴ አገዛዝ በተለይ ከጣሊያን ሽንፈት በኋላ በአንፃራዊ ሁኔታ የተረጋጋ ነበር፡፡ ማሳያውም ለረጅም አመታት የዘለቀው የአገዛዙ ስልጣን ከሌለው አንፃር ረጅም መሆኑ ነው፡፡ ነገር ግን ንጉሱ አለም ሲቀየር፣ ሀገር ወደ ውጪ እየተመለከተ ሲለወጥ ምልክቱን እንኳ መመልከት አቅቷቸው፣ እኛ በአለም ቢያንስ በግርማቸው የሚፈሩና የሚከበሩ ንጉስ እንደሰማነው በወታደሮች በትራስ ታፍነው ተገደሉ፡፡ ቀዳማዊ ሀይለስላሴ ከስደት መልስ ሀገሪቱን ለማረጋጋት የሄዱበት መንገድ እጅግ አስተዋይ ያስባላቸው ነበር፡፡ ሀገሪቱ ከ1933 ዓ.ም በኋላ በአርበኛ፣ በስደተኛና በባንዳ ተከፋፍላ ለዘላቂ የስልጣን መደላድሉ አስጊ ጊዜ ላይ ነበረች፡፡ እንግሊዞቹ ሳይቀሩ ላራሳቸውም ይሁን ለሌላ ምክንያት ራስ አበበን የመሰሉ አርበኞችን ስልጣን እንዲዙ ቢያበረታቱም ይህንን ጊዜ ለማለፍ ንጉሱ ያለፉበት መንገድ አስገራሚ ቢሆንም ይህ ብልሀታቸው በተለይ አስተዋነታቸው በስተርጅና የት ገባ የሚሉም አሉ፡፡ ድብቅ አባዜ ይሆን ይሆን?
የደርግ ወታደራዊ ስብስብ አብዮቱን ጠልፎ ወደ ስልጣን ከመጣ በኋላ የኢትዮጵያን የተማሪዎችና የሌሎች አብዮተኞችን ትግል መስመር አሳተው፡፡ በሁለት አዋጆች/ደንቦች መሬትን ላረሹ እንዲሁም "ትርፍ" የከተማ ቤትና መሬት ለመንግስት ብሎ አብዮተኛውን በእጅጉ ጥያቄና ምክንያት አሳጣው፡፡ ይባስ ብሎ ዴሞክራሲያዊ መብትን ለመደፍጠጥ መሞከሩ የፈጠረው በተለይ በህቡዕ ከሚንቀሳቀሱ አካላት ጋር የፈጠረው መላተም ብዙዎች ህይወታቸውን የገበሩበትን ክፉ አጋጣሚ ፈጠረ፡፡ አሁንም በደርግ ወታደራዊ ቡድንም ይሁን በህቡዕ በሚንቀሳቀሱት አካላት ውስጥ የራሳቸውም ሆነ ኢትዮጵያዊ የሆነ የድብቅነት ስነልቡና ተጠቂዎች ያደረጋቸው ስሪት እንዳለ ይሰማኛል፡፡ በተጨማሪም የአሸናፊና ተሸናፊው ስልቡና አሁንም ድረስ እያማሰነን ይገኛል፡፡
ኢህአዴግና ሻቢያ ለአመታት የዘለቀ "ከቀኝ ገዢ" ስርአት የመላቀቅና  የራስን ክልል "ነፃ የማውጣት" ጦርነት እንዲሁ በድብቅነት ስነልቡና በተጠናወተው ምክንያት ተሸፍነው ባደረጉት ተጋድሎ አንዷ ሀገር ሁለት ሆነች፡፡ ለዘመናት በድብቅ አጀንዳ ተታሎ ነፃ የመውጣት እንቅስቃሴውን የደገፈው ህብረተሰብም የሌላ ዙር "ቀኝ ገዢ" ሰለባ  ሆኗል ብለው የሚከራከሩ ብዙሀን ናቸው፡፡ የማይታበለው ሀቅ ግን ብዙዎች የስኳር ነገር አልሆን በሏቸው የድብቅ ነፃ አውጪነት ካባቸው እስኪገለጥ ድረስ ሞሰኑ፣ ነቀዙ፣ ተበላሹ ድመት ብትመነኩስም አስተረተባቸው፡፡ ይህም የድብቅ ስነልቡናቸው መገለጫ ሆኖ ወጣ፡፡ ከኢህአዴግ ውስጥ ጊዜው እድል የፈጠረላቸው ከወስጥ ገፍተው ስልጣን ሲይዙ ከውጪ የነበረውን ግፊት በመመልከት የጠለፋ ያህል የጥያቄው ወራሽ ሆነው ብቅ ያሉት እነዚህ አካላት የድብቅ ስነልቦናው ችግር ተጠቂ ይሁኑ አይሁኑ ጊዜ የሚፈታው ጉደይ ነው፡፡
የሚገርመው ነገር ይህ የድብቅነት ስነልቡና ችግር በመንግስትነት ባሕርይ ሁሉንም ሲጎዳ ጎልቶ ይታይ እንጂ አጋጣሚዎች እያሳየን ያሉት ይህ የድብቅነት ስነልቡና በግለሰብ፣ በቤተሰብ፣ በድርጅትና በማህበረሰብ ደረጃ የሚንፀባረቅ ችግር መሆኑን ነው፡፡ ከጓደኝነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከትዳርና ቤተሰብ ምስረት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከድርጅት ባልደረብነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከማህበረሰብ አባልነት እንዲሁም ወኪልነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፡፡ ከአነቃቂ ንግግር አቅራቢነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነ ልቡና፣ ከስራ ፈጠራ ስኬት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከበጎ አድራጎት ተግባር ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከፓርቲ አባልነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፡፡ የድብቅ ስነልቡናው ዝርዝር በየፈርጁ ማለቂያ ሳይኖረው ሊቀጥል ይችላል፡፡ ከተቃዋሚነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከደጋፊነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከፓርቲ መሪነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና፣ ከሀገር መሪነት ጀርባ ሌላ ድብቅ ስነልቡና ዝርዝር ያደክማል፡፡
ለዚህ ጉዳዬ አስረጅ እንዲሆነኝ እስቲ እንድ ምሳሌ ላንሳ፡፡ የሰሞኑ የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን (ኢሳት) ጉዳይ እጅግ የሚገርም ነው፡፡ በየማህበራዊ ሚዲው የሚገልፀውና የሚሰራጨው መልእክት፣ ኢሳት ባለደረቦቹን በአመለካከታቸው ምክንያት የማግለል ስራ እየሰራ እንደሆነ ሲሆን፤ ድርጅቱ ያወጣው ግልፅነት የጎደለው መግለጫ (ለአላማ እንደሆነ በድንብ ስለሚያስታውቅ ኢሳቶች ቢያስቡበት መልካም ነው) ደግሞ የሚያትተው የለውጥ ሂደት እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሆነ ነው፡፡
ኢሳት በሀገሪቱ ለመጣው ለውጥ እንደ ብዙሀን መገናኛ ጣቢያ ዋነኛ ድርሻ እንዳለው የማይታበል ነው፡፡ ብዙዎች ግን ሙያዊ ስነምግባርን በተለመከተ በኢሳት ላይ ጥያቄ አላቸው፡፡ በጊዜው ኢሳት የነፃ አውጪ አይነት እንቅስቃሴ በስሜት ያደርግ ስለነበር ይመስለኛል፡፡  የዚህ አይነቱ የብዙሀን መገናኛ ስነምግባር የማይደገፈው በምክያትና በማስረጃ ከሚያምን ተከታይ ይልቅ ስሜቱን የሚከተል ተከታታይ መፍጠሩ ነው፡፡ የሚገርመው ይህ ተከታታይ ሁኔታዎች የተቀየሩ ዕለት በራሱ በጣቢያው ላይ መነሳቱ የማይቀር ነበር፣ እንሆ ሆነ፡፡
የለውጡን መምጣት ተከትሎ በኢሳት ውስጥ በተለይ በተፅእኖ ፈጣሪነታቸው የሚታወቁት ግለሰቦች የለውጡ ግልፅ ደጋፊ ሆነው መምጣታቸው ባያስገርምም፣ በኢሳት ውስጥ ለሀሳብ ልዩነት የሚሰጠው ቦታና ግምት እንደተወራውና እንደተዘመረው እንዳልነበር የሚያሳዩ ነገሮች ከለውጡ መምጣት ማግስት ጀምሮ መከሰት ጀምረው ነበር፡፡ ይህም አብዛኛውን ተመልካችና አድማጭ አሁን ከአንድ ዋንጫ መጠጣት ሊቀር ነው፤ የሀሳብ ፍትጊያ የሚያመጣውን ልዕልና ልናይ ነው፤ ያለው አድማጭ ተመልካች በርካታ ነበር፡፡ በእርግጥ በኢሳት ላይ የነበረውን የቆየ የብዙሀን መገናኛ ጣቢያነት ሚናን ያኮሰሱና የነፃ አውጪ ግንባርነት ሚናን ያላበሱ የቀን ተቀን አሰራሮች በብዙዎች ዘንድ አልተዘነጉም፡፡ እንዲሻሻሉ ለማገዝ ያሰበና መሳተፍ የቆረጠ ሰው ቢያንስ በእኔ ዙሪያ እንደነበር አውቃለሁ፡፡  
ነገር ግን አሁን ሁኔታዎች የሚያሳዩት እንደ ሌላው ሁሉ ኢሳትም የድብቅ ስነልቡና ችግር ተጠቂ የሆነ ጣቢያ መሆኑን ነው፡፡ በእርግጥ ከአሀገራቸው ተሰደው የነበሩ ግለሰቦች ወደ አገራቸው የመመለስ እድል ማግኘታቸው አስደሳች ነው፣ ለእነሱም፣ ለቤተሰባቸውም እንዲሁም ለወዳጅ ዘመዳቸው፡፡  ከጥቂት ቀናት በፊት ታማኝ በየነን አንድ ሆቴል ውስጥ በአካል ስመለከተው እኔንም ለየት ያለ ስሜት እንደተሰማኝ ልደብቅ አልፈልግም ፡፡ ከሀገር ከወገን በተለይ የመለየት ሰሜቱ ለኢትዮጵያዊ ካልደረሰብት በቀር ለመረዳት ስለሚከብድ ባልፈርድም  ለማስረዳት ግን ከባድ ጉዳይ የሚሆንብኝ ይመስለኛል፡፡ ለጥቂጥ አመታት ለትምሀርት እንኳ ሀገርን ሲለዩ የሚሰማው ስሜት ባያስቸግረኝም ጎሻሽሞኛል፡፡ ነገር ግን የኢሳት ባልደረቦች በተለይ "ተፅዕኖ ፈጣሪ" ሰዎች ድብቅ አላማ ወደ ሀገር ቤት የመግቢያ እድል ለማግኝት ወይስ እውነተኛ የሰላምና የዴሞክራሲ ስርዓት ለመገንባት የሚደረግ ጥረት ድጋፍ፡፡
የድብቅ ስነልቡና መነሻው ምንም ይሁን ምን ችግሩ ግን ግለፅ ነው፡፡ በመጀመሪያ ግለሰቦች ባለባቸው የድብቅነት ስነልቡና ምክንያት የረጋና የተመቻቸ ህይወት እንዲሁም ውጤታማነት ሲርቃቸው፤ በአንድ አጋጣሚ የሰሩትን መልካም ስራ በሌላ ጊዜ በተቃራኒው እያጠፉ የመኖር አባዜ ውስጥ ይከታቸዋል፡፡ ድርጅቶችም እንደዚሁ ብዙ ድብቅ ስነልቡና ባላቸው ግለሰቦች ተወጥረው የአመፃና የተንኮል አውድማ ሲሆኑ፣ የማደግና የመለወጥ እድላቸው መክኖ ለሌሎች ውድቅና ክሽፈት ምክንያትም ሲሆኑ ይስተዋላል፡፡ ድብቅ ስነልቡና በሀገር ደረጃ ያስከፈለንን ዋጋ ስንመለከተው ከበሽታነቱ አልፎ ሞተን ወደ መቃብር ካልወረድን የማይተወን ክፉ ደዌ እንደሆነብን የተረዳን አይመስለኝም፡፡
በተለይ የወላጅ፣ የአስተዳዳሪ፣ የአመራርና የእናትነት/የአባትነት ሃላፊነት ያለባቸው ሰዎች የድብቅነት ስነልቡናው ችግር ተጠቂነት እየጨመረ መምጣቱ ወላጅ አልባ፣ አስተዳደሪ የማይበረክትለት፣ መሪ ያጣ፣ እጓለማውታን አድርጎን እነሆ ለዘመናት ዘለቀ፡፡ ለመፍትሄው ማን ምን ያስብ ሆን? የድብቅነት ስነልቡና በእኛ ሀገር በሰፊው መገለጫ የሆነው "የጠላቴ ጠላት ለእኔ ወዳጄ ነው" በመሆኑም፤ ጠላቱ የጠፋ ዕለት ወዳጅነትን የሚያዘልቅ አላማም ይሁን ተነሳሽነት ሲጠፋ ይስተዋላል፡፡ "እውቀት የጎደለው ይጎዳል አስተወሎት የጎደለው ደግሞ እጅግ ይጎዳል" ነውና በጠላቴ ጠላት አላማ መስተጋብር የፈጠረ ሁሉ ጠላቱ ሲጠፋ ወይም ሲዳከም አስተውሎ የጎደለው ስለሆነ ከጠላቱ በላይ መበታተኑ መድከሙና መውደቁ ያስገርማል፡፡ ድብው ስነልቡናና አባዜው ማለት ይህ ነው፡፡
ከሙያና ከመስሪያ ቤት ምርጫ ጀርባ ድብቅ ስነልቡና፣ የፖለቲካ ፓርቲ ከማደረጃት ጀርባ ድብቅ ስነልቡና፣ የብዙሀን መገናኛ ድርጅት ከማደራጀት ጀርባ ድብቅ ስነልቡና፣ የበጎ ድራጎት ድርጅት ከማቋቋም ጀርባ ድብቅ ስነልቡና፣ ከሰፈር ልማት አስተባበሪነት ጀርባ ድብቅ ስነልቡና እንዲሁም ሲብስ ጓደኝነት ከመመስረት ጀርባ ድብቅ ስነልቡና ወዘተ... ኢትዮጵያዊነታችንን አውርደውታል፡፡
መድረሻችን የት ይሆን?
ድብቅ ስልቡና የግልፅ ስነልቡና ተቃራኒ ነው፡፡ በግልፅ ንልቡና ሰዎች የምንሻውን እንመኛለን፡፡ እርሱን ለማግኘት እንጥራለን፡፡ ሌሎች ፍለጎታችንንና ጥረታችንን ተመልክተው ሊረዱን ባይችሉ እንኳ ምንገዳችን ላይ በመቆም ደንቃራ ከመሆን ይታቀባሉ፡፡ በዚህ የቀጠለና ያደገ የግልፅነት ስነልቡና ግንዛቤ ባይኖ መማርን፣ ቢሳሳቱ ማረምን፣ ቢበድሉ ይቅርታ መጠየቅን ስለሚያስተምርና በውስጣችን ስለሚያዳብር መለወጥ እንችላለን፡፡ በመሆኑም ግለሰባዊ እድላችን፣ እንደሀገር ፅዋ ተርታችን በተጠናወተን የድብቅ የስነልቡነ ችግር  እንዲቀረፍ ብንተጋ፡፡ ግላዊ አስተሳሰብና አመለካከት ክቡር ሆኖ ሳለ ለድብቅ ስነልቡና የሚዳርገን ችግር በትውልድ ላይ ብንሰራ፡፡ 

አሮጌ ሀሳብን አዲስ ልብስ ማልበስ እንዳይሆን


አሮጌ ሀሳብን አዲስ ልብስ ማልበስ እንዳይሆን
ጌታቸው መላኩ (የሚዲና ተግባቦት አማካሪ)                        

ሰሞኑን አንድ ለውጥ ተኮር በተለይ ድርጅታዊ ለውጥ ተኮር ጉዳይ ላይ ሀሳቤን እንዳካፍ በአንድ ድርጅት ከፍተኛ አመራር ተጋብዤ ነበር፡፡ ግብዣው ሳይገርመኝ አይቀርም፡፡ ምን ትልቅ ነገር ሰርቼ ነው የእኔን ሀሳብ ለመጋራት የተጋበዝኩት የሚል ሀሳብም ውስጤ ይብላላ ጀመር፡፡ ወደ አእምሮዬ ጓዳ በመዝለቅ የተለየ ነገር ፍለጋ ስባክንም ሰነበትኩ፡፡ ወደ መረጃዎቼና መፃህፍቶቼም ማስቀመጫ አልፌ ልዩ ነገር ፍለጋ ቀናትን አጥፈቼ ነበር፡፡ ያላስቀመጡትን ፍለጋ ማለት ይህ ነው!!!
ለማንኛውም ጠሪ አክባሪ ነውና ያለችኝን ለማካፈል ወስኜ ለማዘጋጀት ሳስብ ሁለት አጋጣሚዎች እንደ መልካም አጋጣሚ ተከሰቱልኝ፡፡ አንደኛው የማህበራዊ ብዙሃን መገናኛ ላይ ያየሁት በድርጅቶች አመራር መካከል የትውልድ ልዩነት ሲኖር መስተጋብሩ ምን ይመስላል? ልዩነቱ አሳሳቢስ ከሆነ ምን ማድረግ ይበጃል? የሚል ጉዳይ ነበር፡፡ በዚህም የተለያዩ ታዋቂ የድርጅት ዘላቂ አመራር ባለሙያዎች ያወሱትን ጉዳይ ሳሰላስል ቆየሁ፡፡ በዚያ ላይም ተመርኩዤ ሀሳቤን በማደራጀት ላይ እንዳለሁ ሁለተኛው ገጠመኝ ተከሰተ፡፡
ሁለተኛው ገጠመኝ በኢትዮጵያችን ያሉ በተለይም በዋናነት ከውጪ ሀገር በስደት ቆይተው የዶ/ር አብይ ቡድን ወደ ስልጣን መምጣቱን ተከትሎ በተፈጠረው ምቹ አጋጣሚ የገቡት የፖለቲካ ፓርቲዎች መክሰማቸውን ሰማሁ፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ አዲስ ፓርቲ ለማቋቋም ስብሰባዎች እየተካሄዱ መሆናቸውን ተመለከትኩ እንዳዶቹንም ለመታደም ሞከርኩ፡፡ ነገር ግን አሁንም የታዘብኩት ነገር ቢኖር በኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ አሁንም ፊትአውራሪዎቹ ላለፉት ሰላሳ አመታት ከዚያም በላይ የምናውቃቸው ፊቶች ሆነው ማግኘቴ ነው፡፡ በሰለጠነው አለም የተለመደ እንዲያውም ተቀባይነት ያለው ጉዳይ ይመስለኛል፡፡ የፕሬዚደንት ኦባማ ጊዜ ምክትል ፕሬዚደንት የነበሩት ጆ ባይደን አሁን ደግሞ ለፕሬዚደንትነት ለመወዳደር እየተዘጋጁ እንደሆነ ሰምተናል፡፡ ይህንን ውሳኔታቸውን ተከትሎ በተለያዩ አካላት አይመጥኑም፣ በተለይ ፆታዊ መስተጋብራቸው ስርዓት ይጎድለዋል ያሉ ከሳሾች ቢነሱባቸውን እሳቸው ግን በሀሳባቸው እንደሚገፉበት አስረግጠዋል፡፡
በእኛ ሀገር ግን  ባለፉት አርባ እስከ ስልሳ አመታት ውስጥ በፖለቲካ ትግል ስም የምነዋቃቸው ግለሰቦች አሁንም የአዲሱ ፖለቲካ ምህዳር ዋነኛ ተዋናይ ሆነው መጥተዋል፡፡ ልምድ እጅግ ትልቅ አበርክቶ እንዳለው የማይስተባበል ቢሆንም ከላይ ያነሳሁት የትውልድና ዘመን ልዩነት እነዚህን ግለሰቦች ውጤታማ ያደርጋቸው ይሆን? የሚልም ስጋት ጭሮብኛል፡፡ ከላይ ወደተነሳሁበት ጉዳይ ልመለስና ንፅፅር ለማድረግ በመሞከር እነዚህ ዘመናትን የተሻገሩ አንጋፋ ፖለቲከኞች በአዲሶቹ ፖለቲካ ፓርቲዎች ውስጥ ሊገጥማቸው የሚችለውን ተግዳሮቶች ለማመላከት ልሞክር፡፡
የአመራር ተመክሮ
እነዚህ አዲስ ፓርቲዎችን በነባር መሪዎች ጠርናፊነት ወደ ሜዳው ከገቡ ሊከሰቱ የሚችሉ ተግዳሮቶችን ከመልካም አጋጣሚዎቻቸው መሳ ለመሳ ለማንሳት ልሞክር፡፡ ተግዳሮታቸው የትየለሌ ናቸው ብለው የሚከራከሩ ብዙዎች አሮጌን ሀሳብ አዲስ ልብ አልብሶ ማምጣት ሲሉት፤ የነባር ፖለቲከኞችን ተሳትፎ የሚደግፉት አካላት ደግሞ "ወይን የሚጥመው ሲቆይ ነው" በማለት ይከራከራሉ፡፡ ለማንኛውም ከሳይንሳዊ መነሻ ጉዳዩን ማየት ለግንዛቤም ለገንቢ ትችትም ስለሚጣቅም ከዚያ እንፃር ለማየት ልሞክር፡፡
በመጀመሪ ደረጃ የትውልድ ልዩነት በሚንፀባረቅበት ተቋም ውስጥ የሚንፀባረቁጽ ችግሮች መነሻቸ የልምድና ተመክሮ ጉዳይ ነው፡፡ ቀዳሚው ትውልድ በአብዛኛው ኑባሬያዊና ተዋረድን የጠበቀ አመራርና አሰራር ለማስፈን እንደሚጥር የእስትራቴጂ ሊቁ ዶ/ር ፒተር ሴነጄ ሲናገሩ፤ የኋለኛው ትውልድ ደግሞ በአመራር ፍልስፍናው ከፈጣንና ልዩነትን የሚፈጥሩ እርምጃዎች ላይ ያተኩራል፡፡ ይህም በዶ/ር ፒተር አገላለፅ  (Traditional/Hierarchical leadership Vs. Dynamic and Breakthrough leadership) ይባላል፡፡
እንደ ዶ/ር ፒተር አገላለፅ በጣም ጥቂት መሪዎች ዘመን ተሻጋር የሚባለውን ሁለቱን እሳቤዎች የማቀናጀትና የመጠቀም አቅም ሲኖራቸው ብዙ መሪዎች ግን ሲቸገሩ ይስተዋላል፡፡ በሆኑም በነባር አመራሮች የሚመሰረቱት አዳዲስ ፓርቲዎች የሁለቱን ዘመን ጠቀስ እሳቤና ልነቶች የማቻቻል አቅምና ችሎታቸው መፈተኛ የቤት ስራዎቻቸው ይሆናሉ፡፡
ሁለተኛው የቀዳሚው ትውልድ በአዲስ ትውልድ ፓርቲዎች ላይ የመሳተፍ ተግዳሮት የእሳቤ አድማስ (imagination) ላይ ያለውን ልዩነት በማንፀባረቅ ላይ ያተኮረ ነው፡፡ የእሳቤ አድማስ (imagination) የነገሮችን ሁለንተናዊ ቁመና (ስፋት፣ ጥልቀት፣ አስቸኳይነት፣ ምስጢራዊነት፣ ጊዜ ተሻጋሪነትና) የመሳሰሉትን ነገሮች ያካተተ ነው፡፡ በመሆኑም ይህ የእሳቤ አድማስ ልዩነት የጉዳዮችን ትርጉም በግልፅ በትውልዱ መካከል ይፈጥራል፡፡ ይህም ለመግባባትና ልዩነትን ለማቻቻል የሚደረጉ ጥረቶች ጥግ ድረስ የመጓዝ ፈቃደኝነት ኖሮ መልካም መግባባት ቢኖርም፤ ሁለግዜ የሚሳካ ጉዳይ ሊሆን ስለማይችል ልዩነቶች ከባድ ሆነው በሚመጡበት ጊዜ ድርጅታዊ አቋም ሊፈተሽ ይችላል፡፡
ለውጥን በበጎ የመመልከትና የመሻት ጉዳይ (adaptation to change)
ለውጥ የማይቀር ጉዳይ እንደሆነ በርካታ ምሁራን የሚስማሙበት ጉዳየ ሆኖ ሳለ፣ የማትቀረውን ለውጥ መፍራት ወይም ለመከላከል መሞከርን ነባራዊ ተቃርኖ (Existing paradox) ይሉታል፡፡ ምሁራን የመሪዎችን ስራ መፈተሻ መሰንክልም ይኸው ለውጥ እንደማይቀር እየታወቀ የሚፈተር መከላከል ነው፡፡ ምሁራን በለውጥ ጊዜ የሚተሉትን የመከላከል ግባራትን የማክሸፊያ መንገዶች ብለው ካስቀመጧቸው ስልቶች መካከል የለውጥ አካላትንና ተዋንያንን የስሜት ደረጃ በመከታተል ሃለፊነትን መወጣት ሚለው ቀዳሚ ቦታ ይሰጠዋል፡፡ በመሆኑም ተዋንያንን የመምራት ጉዳይ እጅግ አስፈላጊና አስትራቴጂዊ ጉዳይ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ይህም ለውጥን በበጎ ለመመልከት የመሻት ሁኔታን ይፈጥራል፡፡
አሮጌ ሀሳብን በአዲስ ልብስ የመምጣቱ ፍርሀት በእኛ
ከግማሽ ደርዘን በላይ ፓርቲዎች ከስመን (እስካሁን ህጋዊ ስርአቱ ተጥሷል የሚለው ጭቅጭቅ ባይቋረጥም) አዲስ ህብረ ብሄራዊ ፓርቲ አቋቁመናል ካሉን ሳምንታት ተቆጥረዋል፡፡ በዚህም ጊዜ አንደ ሁለጊዘው በርካቶች በተስፋ ትቂቶች ደግሞ በጥርጣሬ ከዚያም ያነሱት ደግሞ በፍርሀት ጊዜ የሚያመጣውን እየጠበቁ ይገኛሉ፡፡ ተስፈኞቹ በአብዛኛው ትንታኔ ሳይኖራቸውና ሳያሻቸው "መልካሙን ነገር የሚያመጣው ፈጣሪ ነው" ብለው የሚያምኑ እንደሆነ ያደረኩት ጥቂት ግምገማ አሳይቶኛል፡፡ ቀሪዎቹ በአዲሱ ፓርቲ መሪዎች ልምድና ተመክሮ ሚተማመኑ ይመስላሉ፡፡  በጥርጣሬ ሁኔታውን የመከታተሉት ደግሞ የሀገራችን ፖለቲካ ከልምድ ከሚገኝ ብስለት ይልቅ ደራሽ ስሜት የሚነዳው ሆኖ ስላገኙት መጠርጠርን መርጠዉ ሚተባበቁ ይመስላሉ፡፡ እነዚህ አካላት ሁኔታዎች ባይሳኩ ማንንም ምክንያት አድርገው ማማረር የሚፈልጉ አይመስሉም፡፡ ይልቁንም በሂደት ሌላ አማራጭና ችግር መፍቻ ዘዴን የሚስቡ ይመስላሉ፡፡ "ፈሪዎቹ" የሰለባዎች ስነልቡና ምርኮኛ የሆኑ ይመስላል፡፡ በእነዚህ ግለሰቦች ላይ ሀሳብ የመስተት ማንም የሞራል የበላይነት ያለው አይመስለኝም፡፡ ይልቁን ጠባሳቸው ለሌሎች ትምህርት ሆኖ እንዲታይ መፈለግ አዝማሚያ ያሳያሉ፡፡
በመጨረሻም የለውጡ ሂዳት በግለሰብ አመራር ላይ ብቻ የሚንጠለጠል እንዳልሆነ ይታወቃል፡፡ ነገር የመሪዎች ግንዛቤና አቋም ደግሚ አይነተኛ ጉዳይ ነው፡፡ በመሆኑም የአዲሱ ፓርቲ መሪ ነባር ታጋዮች ዘመናቸውን መዋጀት ዋነኛ ስራቸው መሆኑ የሰማኛል፡፡ መፅፉም ዘመኑን ዋጁ ይለናልና፣ እዩት መርምሩት አስፈላጊውን ጉዳይ ለዩና ስሩበት ማለት የመስለኛል፡፡
ልቡና ለመሪዎቻችን ዘመናቸውን እንዲዋጁ!!!