Thursday 17 May 2018

ዶ/ር አብይ አህመድ ፓርላማ ንግግር አንድምታ
ጌታቸው መላኩ
ዶ/ር አብይ አህመድ በፓርቲያቸው የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዬታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ተመርጠው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በመቅረብ ቃለ መሀላ በመፈፀም የርዕሰ መስተዳደሩን ቢሮ ከአቶ ኃይለማርያም ደሣለኝ መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም መረከባቸው ይታወሳል፡፡
ዶ/ር አብይ በጠቅላይ ሚኒስትርነት መሀላቸውን በመፈፀም በይፋ ስራቸውን ሲጀምሩ ባደረጉት ንግግር በደምሳሳው በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ልብ ውስጥ ያለን ጉዳይ ነክተዋል በማለት ብዙዎች ሲያመሰግኗቸው ለማስተዋል የግዴታ የማህበራዊ ብዙሀን መገናኛ መንገዶች አባል ወይም ተጠቃሚ መሆን አይሻም፡፡ ግለሰቡ ኢትዮጵያዊነት ከሚለው ትልቁ ጉዳይ አንስተው በየስራ ዘርፋችን ባለፉት ጊዜያት ያሳለፍነውን የባከነ ጊዜ የትርፍ ሰዓት ሥራ ለመስራት እንድንተጋ አሳብበውናል፡፡ ይኸውም በዋናነት በተለይ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች በተከሰቱ ተቃውሞዎች የባከኑ ጊዜያትን ያመላከተ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ነገር ግን በሶማሌና በኦሮሚያ ክልሎች አጐራባች ነዋሪዎች እንዲሁም በሌሎች መለስተኛ ችግሮች የተነሱባቸውን የደቡብና የጋምቤላ ክሎችንም የሚያካትት እንደሆነ ግን ለማጤን ጉዳዩን ለተከታተለ ሰው በግልፅ የሚታየው ጉዳይ ነው፡፡ ሆኖም ጠ/ሚው የተጎዱ ወገኖችን ለማሰብ በዚህ ንግግራቸው ቢኖርም መዘግየታቸው ምን አለ እንድንል ያሳስበናል፡፡
የንግግራቸው ልዩነት ለእኔ በተለየ ባይሰማኝም ብዙ አድማጮች ከሌሎች ቀዳሚ መሪዎች (በተለይ በኢህአዴግ) ዘመን ተዘውትረው አልተሰሙም ያሏቸውን ገለፃዎችና ቃላት ስለሰሙ እንደሆነ ብዙዎችን አነጋገሬ የተገነዘብኩት ጉዳይ ነው፡፡ ይህን በይበልጥ ለማየት የንግግራቸውን የመገመሪያ ሶስት ደቂቃ ይዘት በመዳሰስ የሚቀጥለውን ንባብ ለማቅረብ ገፋፍቶኛል፡፡ ይህ የንግግር ትንታኔ አሰራር በሌላው አለም ከተራ ትንታኔነት አልፎ አመላካች ተግባርና በከፍተኛ ደረጃ ትምህርት ጭምር የሚሰጥበት ዘርፍ እንደሆn (though not like cryptology) ማሳሰብ እወዳለሁ፡፡ በሀገራችንም ቢለመድ የተሻለ ግንዛቤ ያመጣል፡፡
ዶ/ር አብይ የመጀመሪያ ነጥብ አድርገው ያነሱት የሥልጣን ሽግግሩ የመጀመሪያው ሰላማዊ ሽግግር እንደሆነ በማስመር ነው፡፡ ነገር ግን ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሣለኝ ስልጣናቸውን የለቀቁት የተፈጠረ ችግር ስላለ የመፍትሔ አካል ለመሆን አስበው እንደሆነ የገለፁትን ለማስተባበል የመጣ አነጋገር ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ ጠ/ሚ ሀይለማርም ከስልጣን አልወርድም ቢሉ ምን ይፈጠር ነበር? እርሳቸውስ ስልጣን የለቀቁት ፈልገው ነው ወይስ ተገፍተው? ስልጣን ባይለቁ ምን ይከሰት ነበር? እውነትስ አንድ የፖለቲካ መሪ አይደለም ክፍል አለቃ የሚፈተነው አስቸጋሪ ሁኔታዎችን በመጋፈጥና በቆራጥ አመራር በመሻገር አይደለምን? ታዲያ ጠ/ሚ ሀይለማርያም ምን ነክቶአቸው ነው አንደዚህ በድንገት ዘጭ ያሉት፡፡ እዚህ ላይ ግልፅ ጦርነት አለመኖር የሰላም መኖርን አያመላክትም የሚለውን አባባል ልብ ይላል፡፡ የዶ/ር አብይ ንግግር ዝግጅት በዚህ መልክ መጀመሩ ግን የተለመደ መንገድ ስለሆነ የተለየ ነው ለማለት ይከብደኛል፡፡
የዶ/ር አብይ ቀጣይ የንግግር ይዘት ይህንኑ ጉዳይ በማንሳት የጠ/ሚ ኃይለማርያም ስልጣን የመልቀቅ ጥያቄን ለግለሰቡ የመከበር ጅማሮ እንዲሆን በሚያሳስብ መልኩ አስቀምጠዋል፡፡ ጉዳዮች በጊዜ ሂደት የሚጠሩ ቢሆኑም የመፍትሄ አካል ለመሆን በኢህአዴግ ውስጥ የተለየ ሰው በመምረጥ እንዴት ይመጣል የሚለውን ለመስማት በደርግ ዘመን የተፈጠረውና ሁሉም የደርግ ባለሥልጣናት ኮ/ል መንግሥቱን ጨምሮ አናውቅም ያሉት የ60ዎቹ ሰዎች ግድያ በደብዳቤ ተደግፎ በቅርቡ ይፋ እንደሆነ እንዳየን ልብ ይሏል (የደብዳቤ ማስመሰል ሊኖር እንደማይችልም እጠራጠራለሁ)፡፡
በሦስተኛ ደረጃ ዶ/ር አብይ ያተኮሩት በሥልጣን ሽግግሩ የተጉትን ማመስገን ላይ ነው፡፡ እዚህ ላይ ዶ/ር አብይ በግልፅ የጠቆሙት ግለሰብ ወይም ቡድን ባይኖርም የኢህአዴግ ምክር ቤትንና የእህት ድርጅቶችን በተለይም ለእሳቸው በፍጥነት ለዚህ መታጨት የተጉትን የሚመለከት ይመስላል፡፡ ዶ/ር አብይ ከኢህአዴግ ም/ሊቀ-መንበርነት ወደ ሊቀ-መንበርነት ሲመጡ ለማ መገርሳ ወደ ፌዴራል ስልጣን ለመምጣት በተግበራ የማይገድ በሂደት ግን አወዛጋቢ ሊሆን የሚችል ህጋዊ ሁኔታ ስላለ ቢመስልም ኢህአዴግ ለህግና ለስርዓት ባይሆን ከአሁን በኋል ግድ እነደሚኖረው ለማሳት እንደሚችል በመለየት ነው፡፡ እዚህ ላይ ታዲያ ተመዞ የሚወጣው ጉዳይ እውነተኛው የኢትዮጵያ ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ ወይስ አቶ ለማ? ነገር ግን አንድ ነን ካሉ አንድ ነን፡፡ እዚህ ላይ በዶ/ር አብይ ንግግር ላይ የቃላት መደነቃቀፍ እንዳለ ያጤነ ሰው ካለ ሌላም ግንዛቤ ሊወስድ ይችላል፡፡
በመቀጠል ዶ/ር አብይ የሥልጣን ሽግግሩን “አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ የመጀመሪያ ሌላ እድል” ሲሉ ገልፀውታል፡፡ አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ከምን አንፃር? የሚለው የሁሉም ጥያቄ ቢሆንም ዶ/ር አብይ በደፈናው የመግባባትና የአንድነትን ስሜት የመገንባት ጉዳይ በሚል አልፈውታል፡፡ አድማጭ ግን የበለጠ ጠልቆ መጠየቅና መመርመር ይገባዋል፡፡
አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ከምን አንፃር ከርዕዬተ-አለም ለውጥ ወይስ ሌላ? ያልታሰበ ጉዳይ አለ፡፡ እዚህ ላይ ጠ/ሚ ኃይለማርያም የድርጅት አባል ያልሆኑ ባለሙያዎችን የመሳብ ሥራ እንደ ጀመሩ ዶ/ር አብይ ደግሞ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትን ወደካቢኔ ለመሳብ አስበው ይሆን እንዴ? የሚል መላምት ቢታሰብ አንደሀሳብ መልካም ይመስለኛል፡፡ ይህስ ቢሆን አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ሊያስብል የሚችል ነገር ይኖረው ይሆን?
ዶ/ር አብይ “አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ የመጀመሪያ ሌላ እድል” ሲሉ ከዚህ በፊት የነበሩት እድሎች የትኞች ይሆኑ? አንባቢ ማጤን ያለበት የተባለው አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ከሆነ ብያኔው ከስልጣን ሽግግር ባለፈ የተለየ መንገድን መከተል ወይም የተለየ አመለካከት ያለውን ተቃዋሚ/ተፎካካሪ የመቀበልና የማሳተፍን ጉዳይ ይመለከት ይሆን? ሌላ እድልስ የተባለው ከየትኞቹ ያለፈ እድሎች አንፃር ነው? 1997 ምርጫ፣ የጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ህልፈት፣ የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት፣ የደርግ መንግሥት ውድቀት? የትኛው? ለትርጉም የቸገረ አገላለፅ ነገር ግን የታሰበበት! በእኔ ግምገማ የዶ/ር አብይ ንግግር ዋናው ማጠንጠኛው ይህ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡
ለማጠቃለል ዶ/ር አብይን ያመጣቸው እድል ወይስ ትጋት? ትልቁ ጥያቄ ነው፡፡ እድል እንዳመጣቸው የሚያምኑ ከሆኑ እድላቸውን በመጠቀም ለራሳቸው የተሻለ የሚሉትን ለመስራት እንደሚተጉ ግልፅ ነው፡፡ ዋናው ነገር “የተሻለ” የተባለው ነገር ለሁም “የተሻለ” እንዲሆን መመኘት ነው፡፡

No comments:

Post a Comment